
አርሰናል የ 25 ዓመቱን የኋላ መስመር ተጫዋች አሌክሳንደር ዚንቼንኮን ከማንችስተር ሲቲ ማስፈረማቸው ይፋ ሆኗል ።
ለዝውውሩ ወደ ሰላሳ ሁለት ሚልዮን ዩሮ ወጪ እንደሆነ ሲገለፅ ቀድሞ በሲቲ ቤት ከሚያውቀው አሰልጣኝ ሚኬል አርቴታ ጋር ዳግመኛ አብሮ የመስራት ዕድልንም አግኝቷል ።
የሀያ አምስት አመቱ ዚንቼንኮ በዚህ ሳምንት ሁለት የጤና ምርመራዎችን አድርጎ በተሳካ ሁኔታ ሲያልፍ የሚቀጥሉትን አራት አመታት በአርሰናል የሚያቆየውን ውል እንደተፈራረመ ተገልጿል ።
ዚንቼንኮ በተከላካይ መስመር እንዲሁም በመሀል ሜዳ ስፍራ ላይ መጫወት የሚያስችል ብቃት ያለው ተጫዋች መሆኑ ይታወቃል ።
ዚንቼንኮ በማንቸስተር ሲቲ ፕሪሚየር ሊጉን እና ካራባኦ ዋንጫን አራት አራት ጊዜ ሲያነሳ አንድ ጊዜ ደሞ የኤፌ ኤ ካፕ ዋንጫን አሳክቷል ።
መድፈኞቹ ከዚህ ቀደም ከማንችስተር ሲቲ አጥቂውን ጋብርኤል ጄሱስን ማስፈረማቸው ይታወሳል ።
መድፈኞቹ በዝውውር መስኮቱ አስቀድሞ ጋብሬል ጄሱስ ፣ ማርኪኖህስ ማት ተርነር እና ፋቢዮ ቬራ ማስፈረማቸው የሚታወስ ነው ።

የልጅነት ህልሜ እውን ሆኗል “
የአርሰናሉ አሰልጣኝ ሚኬል አርቴታ አሌክሳንደር ዚንቼንኮ መድፈኞቹን መቀላቀሉ ደስተኛ እንዳደረገው በሰጠው አስተያየት ተደምጧል ።
” የቡድን ስብስቡን ስለተቀላቀለ ደስ ብሎኛል አሌክስን ከዚህም በፊት በደንብ አውቀዋለሁ ፣ ከሲቲ ከተለያየሁ በኋላም ስፈልገው ነበር ጥሩ ብቃት ያለው ተጫዋች ሲሆን ለቡድናችን ጥራትን ይጨምራል ።
በተለያዩ ስፍራዎች መጫወት መቻሉ ለቡድኑ የማጥቃትም ሆነ የመከላከል ስራ እንደሚያግዘን አምናለሁ ፣ እንደ ግለሰብም አሌክስ ጥሩ ስብዕና ያለው ተጫዋች ነው ” ሲል አርቴታ ሀሳቡን አካፍሏል ።
ዚንቼንኮ በበኩሉ ” በመጀመርያ የልጅነት ህልሜ እውን ሆኗል ፣ ልጅ እያለሁ የአርሰናል ደጋፊ ነበርኩ በተለይ ቴሪ ሄንሪ እና ወጣቱ ሴስክ ፋብሪጋስ ሲጫወቱ ማየት ያስደስተኝ ነበር ” ሲል ተደምጧል ።
Leave a comment