ገጣሚ ህሊና ደሳለኝ

ጠላቴነው ብለህ ባልበዘበዘበት አስረህ ከምታሸው፣
ግዴለህም ጎበዝ እስኪ መጀመሪያ ፈታሹን ፈትሸው፣
የሸንጎ ጠብ ጠና ዳኛ ባከረረው ፣
ሀገር ይጫረሳል ገላጋይ በጫረው፣
ገዳዪም ዋይ ዋይ ነው የሞተበትም ዋይ፣
እንዴት እንሰረው መቃብሯን ታቅፎ የሀገሬን ገዳይ።
አይችለው የለ እንጂ – የልባም ትከሻ፣
ከውርደቱ ደጃፍ – ነውሩን ማምለጥ ሲሻ፣
ገርፎ ማሳመን ነው፣ የፈሪ ሰው በትር፣ የሽንታም ሰው ጋሻ።
እንመን ግድ የለም…
ፍትሕ አይታለምም – ሐቁን እየሸሹ፣
የጠፋው እንዲገኝ፣ እስኪ መጀመርያ፣ ይፈተሽ ፈታሹ፤
አቀርቅራ ታዝግም፣ ትጎናበስ እንጂ፣ መሔድ እስኪያድላት፣
ሰብረህ ስታበቃ፣ ‘ምርኩዝ እንቺ’ ብለህ ደርሰህ አትደልላት፤
‘በኔ ብቻ’ በሽታ – ጥበት እየቀጣን፣
በ’ናታችን ርስት፣ ባባታችን መሬት፣ መደገፊያ እያጣን፤
ቁልቁል እያሰቡ – ምንድነው ከፍታ፣
መብት እየነጠቁ – ምንድነው ግዴታ?
እስከ መቼ ተረት – ምንድን ነው ይነጋል፣
መንገድ እየቀሙ – ምርኩዝ ምን ያደርጋል?
አንተ እንደሁ ልማድህ አለስልሶ መግደል አሳስቆ መግፋት፣
‘ካብኩ’ እያሉ ‘ማቅለል’ ‘ሳምኩ’ እያሉ ‘መትፋት’፣
የበደል ላይ ጀግና – ሬሳ ላይ መዛት፣
መዋረድን ሽሽት – የአሽቃባጭ አፍ መግዛት፤
እየሸሹ ትግል – እየሮጡ ዛቻ፣
በጉንዳን ልቡና – የነብር ዘመቻ፤
የበላ እያሠረ – የቀማ ቢገፈው፣
የሳተ እያረመ – ያጠፋ ቢገርፈው፤
ጀግና ልማዱ ነው፣ ባርያ ሆኖ ታሽቶ፣ ንጉሥ ኾኖ መግዛት፣
እያነሰ ገዝፎ – እየሞተ መብዛት፤
ያ ሽንታም ላመሉ – በሬሳ ይፎክራል፣
ከፈሪ ገዳይ ‘ድል’ – የጀግና ‘ሞት’ ያምራል፤
ይልቅ……
በእኔ ልቅደም ትርክት- የዘር ደዌ አያጥቃን፣
ከጎጥ ቀንበር ፍቱን – ጠቦ መሞት በቃን፤
የጸደይ ወይን ኾኖ – የሐቅ እንባ ቢጥም፣
በድሎ መጀገን – ጀብድ ሆኖ ቢረግጥም፣
የትግላችን ልኩ – ያሳር ደም ቢያስምጥም፣
በሰፋ ሀገር ጠበን – ኢትዮጵያን አንሰጥም!!!
Leave a comment